‎የጎፋ ዞን ግብርና መምሪያ የ2017/18 ዓ/ም ግብርና ዕቅድ አፈፃፀም ግምገማ እና የ2018/19 ዓ/ም የመኸር ዕቅድና የአረንጓዴ አሻራ ንቅናቄ መድረክ የመዋቅር የግብርና ጽ/ቤት ኃላፊዎችና ባለድርሻ አካላት በተገኙበት በሣውላ ከተማ አካሂዷል።

‎የጎፋ ዞን ግብርና መምሪያ ኃላፊ አቶ ዳንኤል ደግፌ እንደተናገሩት የግብርናው ዘርፍ የኢኮኖሚ ዕድገት ለማምጣትና ድህነትን በመቀነስ ረገድ ወሳኝ ድርሻ ያለው በመሆኑ በዕቅድ መመራትና አፈፃፀሙን መገምገም እንዳስፈለገ ገልፀዋል።

‎አክለውም በ2017/18 ዓ/ም ግብርና ዕቅድ አፈፃፀም በአዝርዕት ሰብሎች፤ሆርቲካልቸር፣ነባር እንክብካቤ ከታቀደው 91,034 ላይ 91,941 በመፈፀም 100% ማሳካት መቻሉን ተናግረዋል።

‎አቶ ዳንኤል አያይዘው በአፈፃፀሙ በቴክኖሎጂ አጠቃቀም ላይ ያሉ ክፍተቶችን በመቅረፍ በሙሉ ፓኬጅ የመጠቀም ባህልን በማሳደግ በቀጣይ ምርትና ምርታማነትን ለማሳደግ ይሰራል ብለዋል።

‎በቀጣይ እንደከዚህ ቀደሙ የአረንጓዴ አሻራ ውጤታማነት በቀጣይ ስራዎችን በህዝብ ማዕበል በማጀብ እንዲሁም ለክትትልና ቁጥጥር እንዲመች በሣይት ልየታና በመረጃ ቋት በማስገባት ለውጤት ይሰራል ብለዋል።

‎የጎፋ ዞን ግብርና መምሪያ አደጋ ስጋት ኃላፊ አቶ ያዕቆብ ዘካሪያስ በበኩላቸው እንደተናገሩት የግብርና ስራ በዋናነት በምርት ራስን በመቻል ከተረጂነት ለመውጣት መስራት በመሆኑ በትብብርና በቅንጅት እንሰራለን ብለዋል።

‎አቶ ያዕቆብ አያይዘው በየመዋቅሩ በአደጋ ጊዜ ቀድሞ ለመድረስና ራስን ለመቻል በህዝብ በማሳረስ ምርት እየተሰበሰበ እንዳለና ግንዛቤው ግን በቂ እንዳልሆነ ገልፀዋል።

‎በየመዋቅሩ ከተረጂነት ለማላቀቅ ሀብት አግኝተው የተሸጋገሩ የማህበረሰብ ክፍሎች ወደ ቀደመ ድኅነታቸው እንዳይመለሱ ክትትልና ቁጥጥር ማድረግና በቀጣይ ሌሎችንም በማሸጋገር ከተረጅነት መላቀቅ አንደኛ ግባችን አድርገን እንሰራለን ብለዋል።

‎ከየመዋቅሮች የመጡ አመራርና ባለሙያዎች በሰጡት ሃሳብ ባለፈው አፈፃፀም በጠንካራ ጎን የተፈፀሙትን በማስቀጠል በቀጣይ የታቀዱትን ለመፈፀም የጋራ ስምምነት ላይ በመድረስ መድረኩ ተጠናቋል።